Sunday, April 29, 2012

“የሀበሻ ጀብዱ”

ከተፃፈበት የቸክ ቋንቋ ርዕስ Habešská Odyssea “የሀበሻ ጀብዱ” በሚል የተተረጎመውን መጽሀፍ በተመስጦ አነበብኩት:: መጽሀፉን የጻፉት ቸኮዝሎቫኪያዊው (በድሮው) ብዙ ጊዜ እንደተለመደው “ታሪክን እና ማህበረሰብን እናጠናለን” በሚል ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት መዛግብትን በማስተርጎም እና ቃለ-መጠየቅ በማድረግ በየሚያሳትሟቸው መጻህፍቶቻቸው ስለ ኢትዮጵያ እንደሚዘባርቁት ሳይሆን ከዚህ በተለየ ምክንያት ፈታኝ በሆነ ሰዐት ኢትዮጵያ ተገኝተው በብዙ የጦር ውሎዎች እና ሌሎች ሁነቶች በአካል ተግኝተው ያዮትን ነው የጻፉት:: አልፎ አልፎ በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ አስተያየት ከሚሰጡ በስተቀር ጸሀፊው ከትንተና እና ማብራሪያ ታቅበው የጦርነት ውሏቸውን እና ገጠመኖቻቸውን በጥሬ መረጃ መልክ አቅርበዋል:: ይሄ ማለት ለታሪክ ተመራማሪዎች በመረጃነት ለትንተናቸው እንደመነሻ የሚሆን እጂግ ጠቃሚ ስራ ነው ማለት ነው:: የታሪካዊ ምርምር አጻጻፍ ክህሎት የሌለውም ቢሆን ከታሪኩ ሊወስድ የሚችላቸው ጠቃሚ መረጃዎች አሉ::




ከኢትዮጵያዊነት እሴቶች ጋር በተያያዘ ሲንጸባረቅ የሚታይ ደግነት : የዋህነት: ፈሪሀ እግዚያብሄር እና እምነት : አልበገር ባይነት: እጂግ በጣም ጥልቅ የሆነ ከነብስ ጋር የተሳሰረ የሀገር ፍቅር: የአሸናፊነት ስነ ልቦና : ታዛዢነት : ታማኝነት : አንድነት: ከልክ ያለፈ ወኔ : ግፍና መከራ ችግር ቻይነት የመሳሰሉትን ስናይ በሌላ በኩል ደሞ ከነውር እና ከሀጢያት እኩል ይቆጠሩ የነበሩ ከኢትዮጵያዊነት እሴት ጋር አይን እና አፈር የሆኑ ነገሮችንም እናያለን:: ከክህደት እና ሀገር አሳልፎ ከመስጠትም በተጨማሪ ከጠላት ጎን ተሰልፎ በገንዘን ተቀጥሮ ኢትዮጵያን የወጋ አለ:: ስግብግብነት አለ:: ወራት ያስቆጠረ ረዢም መንገድ እና እንግልት ተቋቁሞ ህይወቱን ሊሰጥ ትግራይ መሬት የረገጠውን ከከምባታ ከሰላሌ ከሸዋ ከጎንደር እና ከሌላውም የመሀል ሀገር የመጣውን የኢትዮጵያን ሰራዊት ከጣሊያኖች ስንቅ እና ትጥቅ ድጋፍ ጠይቆ ተደራጂቶ የዘረፈ እና ኢትዮጵያን የወጋ ቡድንም አለ:: (ከታች ከነማጣቀሻ ገጹ በጨረፍታ እጠቁማለሁ:: )

የታየው ክህደት የሚያበሳጨውን ያህል ጸሀፊው ቅልጥ ባለ ጦር ሜዳ ላይ በባለ ጎራዴው የኢትዮጵያ ገበሬ እና እስካፍንጫው በታጠቀው የጣሊያን ሰራዊት መካከል በነበረው ግብ ግብ ባለጎራደው የኢትዮጵያ ገበሬ በደም ፍላት እየዘለለ የጣሊያኖቹን አንገት ሲመትር ያዮትን የጀግንነትና የወኔያምነትን ጥግ ያለ ምንም ቁትብነት ስዕላዊ በሆነ ሁኔታ ሲገልፁ የሚሰማ የንዝረት ስሜት አለ:: ለቁጥር የሚሰለቹትን ትተን ሀያ አመት የማይሞላው የአቢቹ ታሪክ ራሱ የሚገርም ነው:: በሀገራችን የሲኒማ ጥበብ ያደገ ቢሆን ኖሮ እንደ አቢቹ እና ደጃዝማች አበራ (የራስ ካሳ ልጂ) ያሉ ወጣቶች ከፈጸሙትም ጀብዱ ካሳዩት ወደር የሌለው መንፈሰ ጠንካራነት በተጨማሪ በማህበራዊ ግንኙነት አንፃር የነበራቸው ግንዛቤ አስተዋይነት እና የሀላፊነት ስሜት --- የጦር አውድማውን እና እንደ ወጣት ያሳዮትን ያመራር ብቃት የሚያንጸባርቅ ደህና ፊልም ተሰርቶበት ለትውልድ ጥሩ አስተማሪ ሊሆን ይችል ነበር::
በነዛ ጀግኖች ትውልድ እና በእኛ በእንዝህላሉ ትውልድ መካከል ያለውን ልዮነት ለመተንተን ሞከርኩ:: ባያረካኝም:: የድሮው ወጣት ወኔ አለው:: የሀገር ፍቅር አለው:: ፈሪሀ እግዚያብሄር አለው:: ምናልባት የባህል ወረራ ሰለባ ካለመሆኑ ጋር የተያያዘ ነገር ይሆናል:: አሁን በግልጽ እንደሚታየው ወይ ወኔ የለም:: ወይ የሀገር ፍቅር የለም:: ወይ እምነት የለም:: ወይ ሁሉም የለም:: እነዚህን ሁሉንም አንድ ሰው ላይ ማግኘት አስቸጋሪ ነው የሚሆነው:: የማህበረሰባዊ አስተሳሰብ እና ትኩረት ልዮነትም ይመስለኛል:: ከስነ-ጥበብ አቅም ከእኛ ቀደም ያሉት የሚያንጸባርቁት ፍጹም ሀገራዊ ስሜት እና ማህበረሰባዊ ፋይዳ ያላቸውን ነገሮች ነው:: ይሄን ለማስተዋል ቀደም ያሉትን የሙዚቃ እና የድርሰት ስራዎች ብቻ ማገላበጡ ይበቃል:: ስለ አርበኝነት ስለ ሀገር ፍቅር ኢትዮጵያውያን ስላደረጉት ደጋድሎ ይዘመር ነበር:: "እንኳንስ በህይወት እያለሁ በቁሜ ለሀገሬ ነጻነት ይዋደቃል አጽሜ"" የተቀነቀነው በ70ዎቹ አጋማሽ ወይ መጨረሻ ነበር:: የተደረገውን ተጋድሎ እየሰሙ ያደጉ ትውልዶች በመሆናቸው የሀገር ፍቅር ስሜት እና ለሀገር መጋደልን በባህሪ ስለወረሱ ይመስለኛል::

አሁን ዘመን ተቀይሯል::ገጣሚያን እና ጻሀፍት የሚያነሱት የሚጥሉት ነገር እንደምታዘበው የፍቅር አርበኝነት ነው":: የወጣቱ ተግባር "ማፍቀር ማፍቀር አሁንም ማፍቀር ነው"በሚል አይነት መንፈስ እንኳን አሁን እና ከአስራ አምስት አመት በፊት የነበሩ የልብ-ወለድ ድርሰቶች "የፍቅር አርበኝነትን" የሚያንጸባርቁ አይነት ነበሩ:: የ"ሀብታም ልጂ" የደሀን ልጂ ስታፈቅር ወይ ሲያፈቅር ወይ የሚወዳትን ልጂ ለማግኘት የተፈጠሩ መሰናክሎችን ሲያልፍ … "እምቡጥ ጽጌሬዳን ለምቅጠፍ እሾሁን ማለፍ ያስፈልጋል” አይነት ትረካ ያስነብቡናል ...." “ ውዴ አንቺኮ ማለት ለኔ ሁለ ነገሬ ነሽ”....”አንተ እኮ ማለት ማለት ‘ድቅ ድቅ ባለ ጨለማ ብርሀን ለመፈንጠቅ እንደምትወጣው ውብ ጨረቃ ነህ ...ህይወቴ ያላንተ ብርሀን አይኖረውም” ያስነብቡና እና መጨረሻ ላይ ገጸ-ባህሪ ጭምር ይገሉና የፍቅር አርበኝነቱም በሞት ተጠናቆ አሳዛኝ እንዲሆን ይደረጋል:: ጨለምተኝነት አና የአቸናፊነት ስነልቦና የማያውቀው ሆኖብኝ ቁጭ ይላል::የድሮዎቹ ወጣቶች የሚያነሱት የሚጥሉት (ሮማንቲሳይዝ የሚያደርጉት ሀገር እና ህዝብን ነው:: ) “አንቺ እኮ ማለት ለኔ” የሚሉት ኢትዮጵያን ነው:: አስተሳሰባቸው ርባና በሌለው ምክንያታዊነት የተበረዘ አልነበረም:: የህይወትን ትርጉም የሚያዮበት መነጸር ኢትዮጵያ ነበረች:: የፍቅር ህይወት የላቸውም ማለት አይደለም:: ለመለያየት ካለመፈለጋቸው የተነሳ ተያይዘው ጦር ግንባር የሚሄዱ ሁሉ ነበሩ:: የሚንቀለቀል የሀገር ፍቅር ስሜት በዛን ዘመን ከእድሜ ጋር እንኳን አብሮ የሚያረጂ አልነበረም:: የጦር ምክር ተደርጎ ለመዝመት ከተወሰነ በኍላ የኢትዮጵያ ገበሬ ወታደሮች በራስ ካሳ ፊት የገቡት ቃል ሁኔታውን የሚያመላክት ይመስላል:: በገጽ 50 ላይ እንዲህ ጽፎታል :-
"አንድ ቆፍጣና በራስ ካሳ የሜዳ ላይ ተንቀሳቃሽ ዙፋን ፊት ቀርቦ ጎራዴውን እያወናጨፈ 'በዚህ ጎራዴ አስራ አምስት አንበሶች ገድየበታልሁ: ሁለት እጥፍ ጣሊያንም እገላለሁ' እያለ ፎከረ:: ከማልረሳው ለመጥቀስ ያህል አንድ አዛውንት ጎራዴያቸውን እያወናጨፉ 'በዚህ ጎራዴ ከእምየ ምኒሊክ ጋር አስር ጣሊያን ገድያለሁ:: አሁንም መቶ እጥፍ ጣሊያን እገላለሁ" የሚለው ፉከራ አንዱ ነው:: ሌላው አንድ በግምት ሀያ አመት የማይሞላው ጎረምሳ ሲናገር "እኔ ወጣት ነኝ: ከዚህ በፊት ጀግንነቴንና ታማኝነቴን ለማሳየት እድል አልነበረኝም:: አሁን ግን ሀገሬን ሊወር የመጣን ጣሊያን እንደ ቆሎ አቆላዋለሁ:: አንዱንም አልምርም ሲል በስሜት ተናገር"" ገጽ 50- 51 [ የሀገር ፍቅር እና የአሸናፊነት ስነ-ልቦናው ከትንሽ እስከ ትልቅ ተመሳሳይ እንደነበረ የሚጠቁም ይመስለኛል]

ሴት ወንድ ሳይል የሚያጠቡ ጭምር እንደዘመቱ የሚያመላክትም መረጃ አለ:-
...በዚህ እንደሞላ ወንዝ እያጓራ በሚጓዝ ጦር ውስጥም እንደነገሩ ሸማ የተከናነቡና በጀርባቸው በቅርጫት ሙሉ የማብሰያ ቁሳቁሶች ያዘሉ ሴቶችም ነበሩ:: የሚጠባ ልጂም የተቸከሙ ታይተዋል..."ገጽ 72

በዘመናችን ያለውን ወኔ ቢስነት ከመመዘን በፊት በዚያን ዘመን የታየውን ከልክ ያለፈ ጀግንነት ምክንያት መጠየቅ ያስፈልጋል:: የዚህ የጀግንነት ሚስጥር ምን ነበር?? ምናልባት ብዙ ትንተና እና ጥናት የሚያስፈልገው ጉዳይ ሊሆን ይችላል:: ብዙ ምርምር የማይጠይቀው ነገር ግን የሀገር ፍቅር ለክብር እና ለነጻነት የሚሰጥ ዋጋ ከምንም በላይ ደሞ በፈጣሪ ላይ ያለ ጠንካራ እምነት ይመስለኛል:: ክርስቲያኑ ከልቡ ክርስቲያን ነው:: እስላሙም እንዲሁ ከልቡ እስላም ነው:: ስለ ነበረው የእምነት ጥንካሬ ያንጸባርቃሉ ያልኳቸውን ልጥቀስ:-

...በጦር ሜዳም ሳይቀር መጸለይይቻላቸው ዘንድ እያንዳንዱ ከፍ ከፍ ያለ ሹም ሳይቀር የራሱን ቄስ የራሱን ነብስ አባት ይዞ ነው ወደ ጦር ሜዳ የመጣው:: ቄሶችም ሆኑ ሼኮች የራሳቸውን የሆኑ ወታደሮች ያላቸው ከመሆኑም በላይ በጦር ግንባር ሜዳም ጠመንጃ ይዘው ይሳተፋሉ …
….በጸሎታቸውም ያገራቸውን ድንበር በማን አለብኝነት ደፍሮ የመጣን የጠላት ሰራዊት ከሀገራቸው ጠራርገው ያወጡ ዘንድ እግዚያብሄር ብርታቱን ሰጥቶ ይረዳቸው ዘንድ ሳይታክቱ በየምሽቷ ይለምናሉ: ይማጸናሉ:: ... ' ጦራችንን ሰብቀን ጎራዴያችንን መዝዘን ጠመንጃችንን አንስተን እናባርራቸዋለን::ገጽ 166-167 [በእግዚያብሄር/በአላህ ርዳታ መሆኑ ነው::]

እንዲህ ያለ የሀገር ፍቅር እምነት እና ጀግንነት በበቀለበት ምድር ላይ ልብ የሚያደማም ከሀዲነት ይስተዋላል:: የሀይማኖት እና የቋንቋ ልዮነት ሳይኖር በህብረት የጣሊያንን ወራሪ ጦር ለመመከት ለኢትዮጵያ የነበረውን ታማኝት( ከኤርትራውያኖች ጭምር -ገጽ 138 ላይ እንደተመለከተዉ) እና ቁርጠኝነት ያህል ክህደትን መርጠው ኢትዮጵያን የወጉም ነበሩ:: ክህደት የአማኝ ህዝብ መገለጫ አይደለም:: ከጣሊያን ጋር የሞተ የትግል ሽረት ትግራይ ላይ ሲደረግ ራሳቸውን እንደሺፍታ አደራጂተው በእምየ ኢትዮጵያ ልጆች ላይ አደጋ የጣሉትን የጣሊያን ቅጥረኞች እና ባንዶች እንርሳቸው እንኳን ቢባል አሁን ያሉት ህወሀቶች እና ደጋፊዎቻቸው የሚሄዱትን አኳሄድ እና ባህሪ ከገንዘብ ጋር ያላቸው ትስስር እና አሁንም ድረስ ያለው ዘረፋ እንዳንረሳ ያደርገናል::

የኢትዮጵያ ጦር በጣሊያን ሰራዊት ለመፈታቱ የሀበሻ ጀብዱ ጸሀፊን ጨምሮ ሌሎች በቦታው ያልነበሩ ሰዎችም የሰጡት አስተያየት አለ:: ጣሊያን የትጥቅ እና ሎጂስቲክ የበላይነት ነበረው:: የጣልያን አየር ሀይል የተጫወተው ሚና አለ:: የመገናኛ እና የመረጃ ችግርም እንደነበረ በዚሁ በሀበሻ ጀብዱ ንባቤ ተረድቻለሁ:: ንጉሰ ነገስቱ ለሰላም በነበራቸው ተስፋ ምክንያት በመከላከል ላይ የተመሰረተ ውጊያ እንዲካሄድ ከማዘዛቸው ጋር ተያይዞ የንጉሰ ነገስቱን ትዕዛዙን ለመቀበል ብቻ ሲባል (ጠንካራ የዕዝ ማዕከላዊነት) ጣሊያኖችን ላይ በከበባ አደጋ መጣል እና ማሸነፍ እየተቻለ ጣሊያን ጊዜ እንዲገዛ እና ራሱን እንዲያደራጂ የሆነበት ሁኔታም እንደነበረ ተረድቻለሁ:: እንደዛም ሆኖ ግን የኢትዮጵያ ሰራዊት በተንቤን የመጀመሪያውን ጦርነት ካሸነፈ በኍላ በሁለተኛው የተንቤን ጦርነት ተሸንፎ እንደገና ሀይሉን አስተባብሮ ማይጨው ላይ ጣሊያንን ሲገጥም ለማሸነፍ ተቃርቦ እንደነበር ጸሀፊው ይናገራሉ:: የትግራይ ሽፍቶች ናቸው የተባሉት ግን ተመሳስለው ገብተው ከኍላ የምየ ኢትዮጵያን ጦር በማጥቃት የኢትዮጵያ ጦር እንዲሸነፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል:: በዛ ላይ ተመሳስለው ገብተው ወሬ እየሰለሉ ለጣሊያን ሲያቀብሉ የነበሩትም እነሱው ናቸው:: ይሔ ደሞ ለጣሊያን ድል ጠቃሚ ሚና አልተጫወተም ማለት አይቻልም::

አሁንም የሀባሻ ጀብዱ ጸሀፊ አዶልፍ ፓርለሳክ እንደሚነግሩን( በቦታው የነበረ እንደመሆኑ የበለጠ የሱ ሊያሳምን ይችላል) ራስ ሙሊጌታ ልጃቸውን (ከፈረንሳይ ሀገር ትምህርቱን አቋርጦ ሊዋጋ የመጣ ልጃቸው ነው) አስከትለው በፈረስ ወደ አሸንጌ እየተሻገሩ እያሉ ተደብቀው ተኩሰው የገደሏቸው ራሳቸውን የትግራይ ሽፍቶች ነን የሚሉ ነበሩ:: የወደቁትን አባቱን ሊያነሳ ከፈረስ የወረደው ልጃቸውም እንዲሁ በነዚሁ “ሽፍታ ነን” በሚሉ ከሀዲዎች እና ከይሲ አልሞ ተኳሾች ነው የተገደለው:: እንደሚገባኝ እንደዚህ አይነቱ ነገር ያለመረጃ ልውውጥ እና ስለላ የተሰራ ላይሆን ይችላል:: አንድ የኢትዮጵያን የጦር መሪ ---ራስን ያህል ነገር ሲገደል ከጣሊያኖቹ የሚኖረውን ሽልማት ልብ ይሏል::

በዚህ ክህደት እና ዘረኝነት ግራ የተጋባው ጸሀፊው የጠየቀው ጥያቄ እና ያገኘው መልስ እንዲህ ይነበባል:-
ከመሀል ሀገር ስድስትና ሰባት ወር ሙሉ ፍዳውን እያየ ሲጓዝ ከርሞ እዚህ የደረሰው ወንድማቸው የነዚህን ሚስኪኖች [ዘራፊ ነን የሚሉትን እና የትግራይን ህዝብ] ህይወትና ንብረት ከጠላት (ለመከላከል የገዛ ህይወቱን አደጋ ላይ ጥሎ: ቤት ንብረቱን በትኖ መከራውን ባየ ለምን ይገድሉታል? ስል በድጋሚ አቶ ኪሩቤልን ጠየኩት …
‘አብዛኛዎቹ የትግራይ ሰዎች ይሄንን የተቀደሰ ሀሳብ ይቃወሙታል’ አለኝና ቀጥሎ ‘አንዳንዶቹ ይሄ ከመሀል ሀገር የመጣው የአማራና የኦሮሞ ሰራዊት በትግራይ ከከረመ ያለውን አዝመራ ከብትና ፍየል ይፈጀዋል በለው ይፈራሉ:: ሌሎች ደሞ ጣሊያኖች እስካሁን የወረሩት የትግራይን ግዛት ብቻ ነው እናም ትግራይን ከጠላት ለመከላከል ብቸኛ መብት ያለው የትግራይ ሰው ብቻ ነው ብለው ያምናሉ:: …
...ቀጥሎም ጣሊያኖች ይኼንን ችግር ጠንቅቀው ስለሚያውቁ በአማራው እና በኦሮሞው ጦር ላይ ትግሬዎች መሳሪያ እንዲያነሱ በሰላዮቻቸው አማካይነት ሲሰብኩና እና የነገር እሳት ስቆሰቁሱ እንደከረሙ ጨምሮ ነገረኝ:: ገጽ 121- 122

ሌላ ቦታ ላይ ደሞ እሱ (አዶልፍ ፓርለሳክ) በነበረበት ቦታ ያጋጠመውን እንዲህ ጽፏል :-
...እኛ [እሱ እና ሌላ አውሮጳዊ] እንዲህ በትዝታ ርቀን ከጦር ሰፈራችን ራቅ ብሎ አልፎ አልፎ ድው! ድው!ደው! የሚሉ የተኩስ ድምጾች እንሰማለን:: እዚህም የትግራይ ሽፍቶች ለዘረፋ ይመጣሉ:: ምን ያድርጉ! ጣሊያኖች በመሳሪያና በገንዘብ ይረዱአቸዋል:: ለዚህም ይመስለኛል በደጃዝማች አበራ ዋሻ ደጃፍ ሁለት አነስ አነስ ያሉ መትረየሶች የተጠመዱት::
የትግራይ ሺፍቶች ብዙ ጊዜ በድፍረት እስከ ጦር ሰፈራችን እምብርት ድረስ ዘልቀው ለመዝረፍ ሞክረዋል:: ሽፍቶችን ከሌላው የባላገር ወታደር መለየት አስቸጋሪ ነው:: ሽፍቶቹም ልክ እንደባላገሮቹ ወታደሮች ሁሉ የሚለብሱት ያደፈ ሸማ ነው:: እና በመጀመሪያ እይታ ማንም ሰው ሽፍቶች መሆናቸውን መገመትም መለየትም አይቻለውም:: ገጽ 149

እንዲህ ያለው ክህደት እና ዝርፊያ ነጻነት ሲመለስ ያስከተለው ነገር እንደሚኖር መገመት አይከብድም:: የአጼ ኃይለስላሴ መንግስት “ሆደ ሰፊነት” በሚል ፈሊጥ በባንዳዎቹ ላይ ሀጢያታቸው እንዲበዛ ባያደርጉም በባዶ እግሩ ትግራይ ድረስ በመከራ ሊዋጋ ሄዶ ክህደት የጠበቀው እና በከሀዲወች በመንፈስም በስጋም የደማው የባንዳ ወገን የነበረባቸውን ቢጎስም እና ብድር ቢመልስ በኍላ መልኩን ቀይሮ የብሄር ጭቆና ታርጋ ተለጥፎለት መጡ:: “የብሄር ጭቆናም” ተብሎ ከቀዳማዊ ወያኔ እንቅስቃሴ ወጣ የሚባለው የባንዳዎች የመንፈስ ልጂ ህወሀት ሊታገል ሲነሳ አሁንም “ትግራይን ነጻ በማውጣት” በሚል ፈሊጥ ነበር:: በትግራይ የነበሩ የአርበኛ ልጆችም የፕሮፓጋንዳውን ምንጭ እና ዘዴ ሳይገባቸው ከህወሀት ጋር አብረው እንዘጭ እንዘጭ ብለው አንዳንዶቹ በስተመጨረሻ ህይወታቸውን አጡ:: አንዳንዶቹ ተባረሩ::


አነሳሴ በመጻሀፉ ላይ ያስደመሙኝን አንዳንድ ነገሮች ማካፈል ቢሆንም እያነበብኩ እያለሁ በማገናዘብ ብቅ የሚል ስዕል የነበረኝን ጥርጣሬ እንድገፋበት አደረገኝ:: ህወሀቶች ከየት እንዴት እና ለምን እንደመጡ የሚጠቁም (እንደጠቆምኩትእንደዛ ተብሎ የተጻፈ የለም ---ስንተነትን ግን የምናገኘው ይሄንኑ ነው::) ሳልጠቅስ ማለፍ እንደሌለብኝ አመንኩ:: ከደርግ በኍላ የአርበኛ ልጆች በነበሩ ጭምር ተከልለው ወደ ስልጣን የመጡት የባንዳዎቹ ልጆች የነበረውን የኢትዮጵያዊነት ስሜት ከነደፉት ጎሳን ያማከለ የፖለቲካ አደረጃጀት ሌላ በ 'ህገ-መንግስት" እና በአዋጂም ጭምር ሊያጠፉት ሞከሩ:: እጂግ በጣም የሚገርመው ነገር በባዶ እግራቸው ለረሀብ እና ለሌሎች ችግሮች ሳይበገሩ ከዘመናዊ ጦር ጋር የተጋደሉትን እና ከሀገር በላይ የማይወዱትን ነብሳቸውን አሳልፈው የሰጡትን በመጥፎ ሁኔታ ስሎ የጀግንነት መጀመሪያ እና መጨረሻ ተምሳሌት የህወህት ታጋይ ይመስል ጧትና ማታ ስለ ህወሀት ጀግንነት በትግሪኛ እና በአማርኛ ተለፈፈ በቴሌዝዥን እና በራዲዮ እንድንሰማ ተደረገ:: በዚህ ሂደት ውስጥ እውነተኛዎቹን ለኢትዮጵያ የደሙትን የሞቱትን ጀግኖች በትግራይ መሬት ከጥሊያን ጋር ሲዋደቁ እዚያው በዱር በገደል የወደቁትን ጀግኖች እንዳይነሱ ተደረገ:: ተርጓሚው በእውነት ይሄንን ስራ ለዚህ ትውልድ በማበርከቱ ትልቅ ስራ ሰርቷል:: በህወህት ዘመን ተወልደው ህወሀት ""ጀግና ነኝ:: ጀግና ተፈጥሮ አያውቅም እያለ"" ሲለፋደድ እየሰሙ ያደጉት እና ዛሬ በወጣትነት እድሜ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲህ ያለውን ስራ እንዲያነቡ መምከር ያስፈልጋል ባይ ነኝ:: አምላክ ብርታትን ሀይልን ይስጠን::


Friday, April 20, 2012

""ሁሉ አይጠየቅም::" "ሁሉ አይነገርም::"...?



""ሁሉ አይጠየቅም::"" ""ሁሉ አይነገርም::"" የሚለውን እሳቤ ወደ ልቤ ልወስደው እልና ታዲያ እንዴት መማማር ወይ መግባባት ይቻላል የሚል ነገር ይመጣብኛል:: ያለ ንግግር በምልክክት መግባባት ቢቻል አንዳንዴ ንግግርን ማስቀረት እርግጥ ይጠቅም ይሆናል:: አይቻልም::

ሰው የሚናገረው ወይ የሚጠይቀው ነገሮችን ለመለወጥ ወይንም መልስ አገኛለሁ ብሎ አምኖም ላይሆን ይቻላል::ጥያቄው እንደጥያቄ መሰንዘሩ ወይ ደሞ መነገር የለበትም ተብሎ የሚታሰበው ነገር በመነገሩ ከእፎይታ ስሜት ባለፈ ; ነገሮችን ለሰው ከማካፈል ስሜት ባለፈ ; ጥያቄየን ወይንም ሀሳቤን በግላጭ ማውጣቴ ቢያንስ ባጋጣሚ ካለማወቅ እና ከግንዛቤ እጥረት የመጣ እንኳን ቢሆን የመማር ዕድሉ ይኖረኛል ብሎ ከማሰብም የመነጨ ነው::

ሰላማዊ ሰልፍ የሚባል ነገር ከወጣሁ ሰንብቻለሁ:: ጊዜ አጥሮኝ ወይ መገኘት ሳልችል ያልተገኘሁባቸው ግን ጥቂቶች ናቸው:: ብዙ ጊዜ የማልሄድበት ዋነኛ ምክንያት የሚያስቆጣን በሀገር ላይ የሚቃጣ የህወሀት ጥቃት እዚህ ውጪ ሀገር በሚደረግ በፔቲሺን እና በሰላማዊ ሰልፍ ይቀየራል ብየ ስለማላምን ነው:: ምንም ያህል እውነት ብንይዝም ምንም አይነት የፍትህ ጥያቄ ብናነሳም በዓለማችን ባለው ነባራዊ ሁኔታ እንደምናየው የዐለም ዓቀፍ ፖለቲካ በመርህ እና በፍትህ የተመሰረቱ ናቸው ብየ ስለማላምን ነው:: በታሪክም ይኸው ነበር ሁኔታው:: አሁን ባለንበት ዘመን ደሞ ችግሩ እየከፋ መጥቷል:: አንዳንዴ እንደ ህወሀት ያለ ቡድን በቀዳሚነት ቅጥ ያጣ ዓለም አቀፍ ርዳታ ተጠቃሚ የሚሆነበትን አገባብ አስቤ አስቤ በመርህ እና በፍትሀዊነት ላይ ያልተመሰረተ የዓለም አቀፍ ግንኙነት ነጸብራቅ ( ወይ አንድ ማሳያ) ከመሆኑ በስተቀር ሌላ ምክንያት አጣለሁ::

ሀገሩን ተቀምቶ እየተዘረፈ በዚያም ላይ በርግጫ እን በጡጫ እየተረገጠ በአፈና ስር ያለው ኢትዮጵያዊን በጥርጣሬ እያዮ ረጋጩን ህወሀትን አንዳንዴ የሚቆጡ እየመሰሉ ርባና በሌለው መግለጫ ሌላ ጊዜ በዝምታ የሚደገፈው ህወሀት ነው:: ምንም እንኳን ተጨባጭ የሆነ ማስረጃ መደርደር ባልችልም ከማየው ነገር ግን የአለም አቀፉ ማህበረሰብ እና ሀያላን መንግስታቶች ምንም ቢያጠፋ ምንም የህወሀት ነገር አይሆንላቸውም የሚል እሳቤ ላይ እደርሳለሁ:: ከህወሀት የህዝብ ፍቅር አለመኖር እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታዛዢነት ጋር ሊያያዝ ይችል ይሆናል ጉዳዮ:: ቁም ነገሩ ግን ህወሀት በኢትዮጵያ ላይ እያደረሰ ያለውን ነገር ሀያላኑ መንግስታትም ሆኑ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አሳምረው ያውቁታል:: የየቀኑ የየዕለቱ ዘገባ አላቸው:: በየአታሸዎቻቸው አማካይነት:: እኛ ታዲያ የሞኝ ፈሊጥ አይሉት ምን አይሉት ልክ እንደማያዉቁ ህወሀት ባወጣው እቅድ ቅደም ተከተል መሰረት አንድ ባንድ ጥፋት ሲያደርስ ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ እናሳውቃለን እያልን በየከተሞቹ ሰልፍ እንወጣለን:: ልክ እንደማያውቁ:: አልዋጥልህ እያለ ከሰልፍ ያስቀረኝ የነበረው ጉዳይ::

ዛሬ ግን ለራሴ የገባሁትን ቃል-ኪዳን አፍርሼ እንደገና ለሰልፍ ወጣሁ:: የሰልፉ ጉዳይ የዋልድባ ነገር መሆኑ እና ቢያንስ በዚህ ጉዳይ ክርስቲያኑ ህዝብ እየተሰለፈ ከሰልፉ ቦታ መሰወር ( በስራ ምክንያትም ቢሆን) እንደሌለብኝ ባምንም ሰልፉ የተደረገው በኦንቴሪዮ መንግስት (የአውራጃ አስተዳደር እንበለው) ፓርላማ እንደመሆኑ የዋልድባ ጉዳይ በእርግጥም የኦንቴሪዎ መንግስት ጉዳይ ይሆናል ለዋልድባ ኬር ያደርጋል ከሚል እምነት አልነበረም:: ይሄ መንግስት ለጩኽታችን እጂግ በጣም ትኩረት ከሰጠ ሊያደርግ የሚችለው ጉዳዮ ለሚመለከተው ዩኔስኮ በካናዳ መንግስት አማካኝነት ለህወሀት መንግስት የተማጽኖ ደብዳቤ ይጽፍ ይሆናል --- እንግዲህ "what is there in it for us?" የሚለውን ከመለሱ ማለት ነው:: በሌላ አነጋገር ፊት ለፊታቸው ስለ ዋልድባ ገዳም የሚጮሑ ኢትዮጵያውያንን ገዳም እንዳይታረስ እና የስኳር እርሻ እንዳይሆን የሚታገሉበት ራሺናሊቲ የህወሀት መንግስት በኢንቨስትመት እና ባህል አንፅር ከሚሰጣቸው ጥቅም ራሺናሊቲ ከበለጠ ነው:: ለማንኛውም ባላምንበትም (በሰላማዊ ሰልፍ) መሄድ አለብኝ ብየ ራሴን ሳላሳምነው አዘዝኩት:: ሄጄም ግን አላፈርኩም ጥሩ ስሜት ተሰምቶኝ መጣሁ:: በተለየ ምክንያት ቢሆንም::

ከምንም ነገር በላይ ያስደሰተኝ የተደረገው ጸሎት ነው:: የኦንቴሪዮ ፓርላማ ፊት ለፊት ሆነን "" ስማነ አምላክነ ወመድሀኒነ"" ስንል ተስፋ ባላደርኩብት እና በማላደርግበት ተቋም ፊት ቆሜ የበለጠ መፍትሄ የሚሆን ሀያል አምላክን በዛች ቅጽበት በዛች ቦታ በማስታወሴ ተደሰትኩ::ከምርም ጸሎት አደረኩኝ:: ጸሎቴ ደሞ አግዚያብሄር ሀገር ቤት ላሉ ልባም እና ደፋር ልጆች የበለጠ ድፍረትን እና ማስተዋልን እንዲሰጣቸው እና ቁጥራቸውን ከእለት ወደ እለት እንዲያበዛው ነው:: የሚያባንኑ የሚቀሰቅሱ እና የሚመሩ ኢትዮጵያውያኖች እዚያው ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲፈጠሩ አያሰብኩ ነበር ""ስማነ አምላክነ ወመድሀኒነ"" ያልኩት::


ሁለተኛ ያስደሰተኝ ነገር የኢትዮጵያውያንን ሙስሊሞች ጨዋነት ዛሬም በማየቴ ነው:: ሀጂ መሀመድ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ ከእኛ ከክርስቲያኖቹ እኩል ስለ ዋልድባ ሊጮሁ እና ወጣቱ ከተጠመደለት የሀይማኖት እና የዘር መከፋፈል እንዴት ስብሮ መውጣት እንዳለበት ሊያስታውሱ ነበር:: በሰል ያለ መልዕክት አስተላልፈዋል:: ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት ወጣቶችም እንዲህ ያሉ ናቸው:: እውቅና እና መቻቻልን የሰነቁ:: ራዕይ ያላቸው:: የሀገራቸውን ጥቅም በምንም አይነት ሁኔታ አሳልፈው የማይሰጡ:: እነኚህ ነገሮች ጸሎት ብቻ ሳይሆን ማህበራዊ ዘመቻም እንደሚያስፈልጋቸው አምናለሁ:: በርዕዮተ ዓለም እና በፖለቲካ እይታ የሚደረገው ውይይት እና ክርክር በይደር ትቶ መጀመሪያ ማህበራዊ ንቃተ ህሊናን ወደ መቀስቀሱ ዘመቻ መገባት አለበት ባይ ነኝ::








Sunday, April 15, 2012

"ውሾን ያነሳ ውሾ ይሁን "?

ምንም እንኳን በአካል ሀገራችን ባንሆንም በመንፈስ እዛው ነን:: በተለይ እንዲህ ባለ የአውደ ዓመት ጊዜ:: በመገናኛ ዘዴው መርቀቅ እና ፍጥነት ምክንያት የመረጃ ልውውጡ የዛኑ ያህል ስላደገ እና የየደቂቃውን ጭምር መረጃ ማግኘት ስለሚቻል አሁን አሁን ሀገራችን ያለነው በመንፈስ ብቻ አይደለም ለማለት ያስደፍራል:: እዛው ያለሁ ያህል የማውቃቸው ጉዳዮች አሉ:: በዓይኔ በብረቱ ካላየሁ የሚባል ነገር ብዙም ትርጉም አይሰጥም በዚህ ዘመን:: እንዳይኔ ወይንም ከዚያ በላይ ሆነው ነገሮችን በሚዛናዊነት በመመዘን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ በትክክል የሚያቀብሉ ወገኖች ሳላሉን::

ትንሳኤ እንደመሆኑ እንደደንቡ ቤት ውስጥ እንዲኖር የሚያስፈልገውን የአውደ ዓመት መሰናዶ አድርጌ በላሁ ጠጣሁ ( እየጠጣሁም ነው በስሱ):: እየተሰማኝ ያለው መሳቀቅ (ብቸኝነቱን ለምጀዋለሁ) ግን እንዲህ እንዳይመስላችሁ:: ብዙ ወገኖቻችን በምን አይነት ሁኔታ እንደሚያሳልፉት እያስታወስኩ ነው:: የዶሮ እና የበግ ዋጋ ውሾን ያነሳ ውሾ ይሁን ተብሎ የሚተው ነገር ሳይሆን የኢኮኖሚ የባህል እና ማህበራዊ አንደምታው መመርመር ያለበት ነገር ነው::

ከቁም ነገር አዘል ቀልድ ጀምሮ እስከ ጠንከር ያሉ ዘገባዎች እና አስተያየቶች ተሰንዝረዋል:: ""እንደ እየሩሳሌም እንዳክሱም ጺዎን ተሳልሜው መጣሁ ዶሮና በጉን"" የሚል መልዕክት አንብቤ ከቀልድነቱ ይልቅ ሮሮነቱ ስላየለብኝ ምን መዐት መቶ ነው ዋጋ እንደዚህ ሰማይ የነካው ከሚል ሀሳብ ጋር ብዙ ቆየሁ:: በኔ እንኳን እድሜ ዶ/ሮ ከ5-10 ብር ባለው ሬንጂ ሲሸጥ አስታውሳለሁ:: ትልቅ የሚባል በግ በ75 እና 80 ሲገዛ አስታውሳለሁ:: እውነት ነው የብሩ የመግዛት አቅም እንደተዳከመ ይታወቃል:: በሁለት አስርት አመታት ውስጥ ግን ከመቶ ፐርሰትን በላይ የብር የመግዛት አቅም ሲወድቅ ምን እንደሚባል አላውቅም:: የሚገርመውን የአብዛኛው ሰው ገቢ ትርጉም ባለው ሁኔታ አለመጨመሩ ነው::

እየሆነ ያለው ነገር በቅንጂት እየተሰራ ያለ ነገር እንደሆነ መገመት ይቻላል:: የማን የማን እጂ እንዳለበትም መገመት ይቻላል:: በበዓል ቀን በግና ዶሮ ገዝቶ ከዘመድ ወዳጂ ጋር መቋደስ ለእርድ እና ለስጋ ያለን ፍቅር ሳይሆን የሚያመለክተው ማህበራዊ ፋይዳውን እና ባህላዊ ፋይዳውን ነው:: ብዙ ኢትዮጵያውያን እጂግ በጣም ደሀ እየሆኑ በሄዱበት ሁኔታ ትርጉም እና ክብር በሚሰጣቸው በዐል የሚገለገሉበት ሸቀጥ ላይ ቅጥ ባጣ ሁኔታ ዋጋ መቆለል በአነስተኛ ገቢ ባላቸው ወገኖቻችን ላይ ሳይሆን በባላችንና በማህበራዊ ግንኙነታችንም ላይ እንደተሰነዘረ ጥቃት መቆጠር አለበት:: ጥቃቱ የሚሰነዘርብን ለመጠቃት የተመቸን ስለሆንን እና ለለውጥ ስላልተነሳሳን ነው:: እንደ ህዝብ ስለማንፈራ እና ምን ያመጣሉ ስለምንባል ነው:: እንዲህ ባለ ሁኔታ መፍትሄው ዶ/ር ኃይሉ አርዐያ በመጨረሻው የፍኖተ ነጻነት እትም በሰጡት አስተያየት እንደሚሉት ""ያስጠቃን ባህላችን ነው:: የባህል ባሪያ ስለሆንን ነው:: ዶ/ሮ በ200 ብር ገዝቼ አላድርም ባህሌ ይቅር"" ሳይሆን የተቀናጀ በማይመስል ምናልባት ግን በደንብ በተጠና እና በተቀናጀ ሁኔታ በባህላችን ላይ ጥቃት እየሰነዘሩ ያሉ ሀይሎችን ለይቶ መታግል ያስፈልጋል::

Blog Archive